Friday, January 12, 2018

ልሂቁ ሐኪም ፕሮፌሰር እደማርያም ጸጋ (1929 - 2010)





በሔኖክ ያሬድ
በኢትዮጵያ የዘመናዊ ሕክምና ታሪክ ሉዓላዊ ሥፍራ ከሚሰጣቸው ጠበብት ሐኪሞች አንዱ ነበሩ፡፡ የማከም ጸጋ፣ የማስተማር ክሂል የተጎናፀፉት ፕሮፌሰር እደማርያም ጸጋ ስኬታማ ሙያዊ ሕይወታቸውን በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በኋላ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በተባለው በ1960ዎቹና 1980ዎቹ በሕክምና ትምህርት ቤት የውስጥ ደዌ ሕክምና ክፍለ ትምህርት ውስጥ አሳልፈዋል፡፡
ሊቅ መምህር፣ ሐኪምና ተመራማሪው ፕሮፌሰር እደማርያም በዓለም ደረጃ ገናና ስም ያጎናፀፋቸው በጉበት በሽታ ላይ በተለይ የሄፒታይተስ ቫይረስ ከኢትዮጵያ አንፃር የሠሩትና ለኅትመት የበቃው ጥናት ቀዳሚው ተጠቃሽ ነው፡፡ ሌሎች ምርምሮቻቸውም ታትመውላቸዋል፡፡ ሌላው እያንዳንዱ የኢትዮጵያ የሕክምና ትምህርት ተማሪ የሕመምተኛ የጤና ገጽታ አመዘጋገብን (medical case report) ሀሁ የቀሰመው የፕሮፌሰር ዕደማርያም ጸጋ ትሩፋት ከሆነው አረንጓዴው መጽሐፍ “A GUIDE TO WRITING MEDICAL CASE REPORTS” መሆኑም ይጠቀሳል፡፡ 

ፕሮፌሰር እደማርያም የሕክምና ከፍተኛ ትምህርታቸውን በካናዳ ሞንትሪያል በሚገኘው ማክጊል ዩኒቨርሲቲ ተከታትለው በ1950ዎቹ መገባደጃ በውስጥ ደዌ እና በሆድ ዕቃ ሕክምና በምሉዕ ብቃት ወደ ኢትዮጵያ በመመለስ ላቅ ያለ አገልግሎትን ሰጥተዋል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የውስጥ ደዌ ሕክምና ትምህርት ክፍል ለ16 ዓመታት በመምራትና በማስተማር እንዲሁም ክፍሉ ልዩ ልዩ ዘርፎች ያሉት የአካዴሚክ ዘርፍ እንዲሆንና የቅድመ ምረቃና የሬዚዳንስ ሥልጠና ፕሮግራሞችን በመዘርጋትም ይጠቀሳሉ፡፡
በእርሳቸው አመራርም በ1971 ዓ.ም. ትምህርት ክፍሉ ከመጀመሪያዎቹ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ክፍሎች የድኅረ ምረቃ ትምህርትን ማስተማር ጀምሯል፡፡
የላቀ አገልግሎታቸውን የተገነዘበው ዩኒቨርሲቲውም በ1973 ዓ.ም. ሙሉ ፕሮፌሰርነት አቀዳጅቷቸዋል፡፡ ከረዥም ዘመን አገልግሎታቸው አንዱ የሕክምና ትምህርት ቤቱ ዲን ሆነው ማገልገላቸው ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕክምና ባለሙያዎች ማኅበርንም በ1970ዎቹ በፕሬዚዳንትነት በመሩበት ወቅት በማኅበሩ አጋፋሪነት በርካታ የጥናትና ምርምር ሥራዎች መከናወናቸው ዓመታዊ ጉባዔዎችም መካሄዳቸው ይወሳል፡፡
ፕሮፌሰር እደማርያም በ1980ዎቹ አጋማሽ ወደ ካናዳ በማምራት ኑሮና ሥራቸውን በዚያው ቢያደርጉም የአገር ቤት ግንኙነታቸውን አላቋረጡም፡፡ በተለይ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የቅድመ ምረቃ ተማሪዎችን በማስተማር፣ የኢንዶስኮፒ ሥልጠናን በውስጥ ደዌና በቀዶ ሕክምና ለተካኑ (ስፔሻሊስቶች) ሐኪሞች ሲሰጡ ነበር፡፡
ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ ለሰባት ዓመታት በካናዳ በግራንድ ፎልስ-ዊንድሶር ኒውፋውንድላንድ በጠቅላላ ሕክምና፣ ከ1993 ዓ.ም. ጡረታ እስከወጡበት 2006 ዓ.ም. ድረስ በሃሚልቶን ሄልዝ ሳይንስ/ማክ ማስተር ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ኤሚሪተስ ሆነው አገልግለዋል፡፡
ከአባታቸው ሊቀ ካህናት አለቃ ጸጋ ተሻለና ከእናታቸው / የተመኝ መኰንን ሰኔ 30 ቀን 1929 ዓ.ም. በጎንደር ከተማ ልዩ ስሙ ባዕታ በተባለ ሥፍራ የተወለዱት ፕሮፌሰር እደማርያም የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በጎንደር ከተማ፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ ከተማ ተከታትለዋል።
ከፍተኛ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባችለር ኦፍ ሳይንስ ካገኙ በኋላ ሜዲካል ዶክተርነትን ጨምሮ ሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪያቸውን ከማክጊል እና ከሉንድ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲሁም በለንደን የትሮፒካል በሽታዎች ሕክምና ትምህርት ቤት በመከታተል በሰነቁት የተለያዩ ትምህርቶች በጠቅላላ ሐኪምነት፣ በውስጥ ደዌና በሆድ ዕቃ ልዩ ሕክምና ሞያዎች የላቀ አገልግሎት እንደሰጡ ገጸ ታሪካቸው ያመለክታል።
ለ23 ዓመት አገልግሎት በሰጡበት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ትምህርት ቤት ዲን በነበሩበት ጊዜ ከስዊድኑ ሉንድ ዩኒቨርሲቲ የፒኤችዲግሪ ያገኙት በክሊኒካል ቫይሮሎጂ (Clinical Virology) ነው፡፡
ነፍስ ኄር ፕሮፌሰር እደማርያም ጸጋ ከአገር ውስጥና ከውጭ አገሮች ካገኗቸው ክብሮችና ሽልማቶች መካከል፣ ከለንደን የትሮፒካል ሜዲስንና ሃይጂን ትምህርት ቤት The Frederick Mergatroyed Prize” ከኢትዮጵያ በሳይንሳዊ ምርምር ስኬት የብሉ ናይል ብሔራዊ ሽልማት (Blue Nile Medal)፣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ንዑድ ሳይንቲስት (Distinguished Scientist) ከዓለም ጤና ድርጅት የተጋባዥ ሳይንቲስት ሽልማት (Visiting Scientist Award) ያገኟቸው ይጠቀሳሉ፡፡
ፕሮፌሰር እደማርያም ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በ80 ዓመታቸው ታኅሣሥ 23 ቀን 2010 .. ለ23 ዓመታት በኖሩባትና በሞያቸው ባገለገሉባት ሃሚልተን ከተማ አርፈው፣ ሥርዓተ ቀብራቸው ታኅሣሥ 28 ቀን በዚያው በምትገኘው በቅድስት ሥላሴ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል።
ፕሮፌሰር እደማርያም ጸጋ፣ ከካናዳዊቷ ባለቤታቸው ፍራንሲስ ጸጋ ሌስተር ሦስት ሴቶችና አንድ ወንድ ልጅ አፍርተዋል
በአሜሪካ ከሚገኙት ከቀድሞ ተማሪዎቻቸው አንዱ የሙያ አጋራቸው / አሰፋ ጄጃው ለአሜሪካ ድምፅ ስለሳቸው ልዕልና እንዲህ በማለት ነበር የገለጹት፡-
‹‹በሕክምና ሞያ እጅግ የተወጣላቸው ሐኪም፣ ለሕመምተኛና ለተማሪ ከፍ ያለ ክብር የሚሰጡ፤ ጥሩ ተማሪ የሚያፈሩና ከእርሳቸው የተሻሉ እንዲሆኑ የሚያደርጉ፣ ተማሪ ሆነን ተሳስተሃል ብለን ደፍረን እንድንናገራቸው የሚያበረታቱን ፕሮፌሰር፣ ለሞያቸው የረቀቀ ክብር ያላቸው ሐኪም የሚለው መጠሪያ ለእርሳቸው የተጻፈ የሚመስል ባለሞያ ነበሩ።››


No comments:

Post a Comment