የኢትዮጵያ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ የቱሪስት መስህቦችን በተገቢው መጠን መጠቀም ቢቻል ኖሮ ድህነት አንገት የሚያስደፋ የዘመናት ዕጣ ፈንታ አይሆንም ነበር፡፡ እነዚህን ድንቅ መስህቦች ታቅፎ ለዘመናት በድህነት ውስጥ ተዘፍቆ መኖር አሁንም እንቆቅልሽ ነው፡፡ ይህች የቅድመ ዘር መገኛ የሆነች በቅኝ ገዥዎች ሳትደፈርና ወራሪዎችን ስትመክት የኖረች አገራችን በተለይ ከአንደኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ በግሪኮች፣ በሮማውያን፣ በፐርሺያውያን፣ በግብፃውያንና በመሳሰሉ ጥንታዊ ተጓዦችና ነጋዴዎች የምትታወቅ ናት፡፡ ታሪካዊ መስህቦቿ የሃ፣ አክሱም፣ ላሊበላ፣ ጎንደር፣  ሐረርና የመሳሰሉት ወደ አገሪቱ በመጡ የተለያዩ አውሮፓውያን አሳሾች ተጎብኝተዋል፡፡ እስካሁንም በድንቅ መስህብነታቸው ይታወቃሉ፡፡ በተፈጥሯዊ መስህብነት ደግሞ ታላቁ የስምጥ ሸለቆና በእሳተ ጎሞራ የተፈጠሩ በርካታ ሐይቆች፣ በ14 ጥብቅ ክልሎች ውስጥ የሚገኙ የዱር እንስሳት፣ አዕዋፋት፣ በአፍሪካ ትልቁ የጣና ሐይቅ፣ የታላቁ የጥቁር ዓባይ ወንዝ መነሻና ሸለቆ፣ ወዘተ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ሁሉን ዓይነት የአየር ንብረት (ደጋ፣ ወይና ደጋ፣ ቆላ፣ ውርጭ)፣ ከዳሎል ኤርታሌ እሳተ ጎመራ እስከ ስሜን ተራራ ቁር ድረስ የቱሪዝም ሀብቶቻችን ናቸው፡፡ እነዚህ መስህቦች ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቁጥር አንድ ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ማድረግ ሲገባቸው፣ የረባ ጥቅም ሳይገኝባቸው ዘመናት ነጉደዋል፡፡ በጣም ያስቆጫል፡፡ ከእንቅልፍ መባነን ያስፈልጋል፡፡
በቅርቡ አገሪቱ በቱሪዝም የምትታወቅበት ‹‹Land of Origins›› የሚባል የእንግሊዝኛ ስያሜ የያዘ ልዩ መለያ መውጣቱ የሚታወስ ሲሆን፣ ባለፈው ሳምንት ደግሞ የአማርኛ አቻ ትርጉሙ ይፋ ተደርጓል፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ምድረ ቀደምት›› የሚባል አዲስ ልዩ መለያ ተገኝቷል፡፡ ላለፉት 50 ዓመታት በሥራ ላይ የቆየውን ‹‹13 Months of Sunshine›› (የ13 ወራት ፀጋ) ተክቷል፡፡ የቱሪዝም ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት አራተኛ መደበኛ ጉባዔ ላይ ይፋ የተደረገው ይህ አዲስ ልዩ መለያ ወይም ብራንድ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው የፀደቀው፡፡ የአገሪቱ የቱሪዝም አባት በመባል የሚታወቁትና ፋና ወጊው አቶ ሀብተ ሥላሴ ታፈሰም ዕውቅናና የወርቅ ፒን ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ ከዚህ በመለስ ግን የሚጠበቅበትን ያህል መንቀሳቀስ ያቃተው የቱሪዝም ሴክተር መሠረታዊ ለውጥ እንደሚያስፈልገው መተማመን ተገቢ ነው፡፡ ቁጭ ብሎ ማንቀላፋት የሚያበቃበት ወሳኝ ጊዜ ላይ ነን፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ በተለያዩ መስኮች ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባት አገር ናት፡፡ ራሷን ከኮሎኒያሊስት ወራሪዎች ታግላ ነፃ የወጣች አገር ሕዝቧ ግን በነፃነት የመኖር መብት አላገኘም፡፡ በተለያዩ ሥርዓቶች በጭቆና ሥር ነው የኖረው፡፡ አሁንም በጣም ብዙ ርቀት ላይ ነው የሚገኘው፡፡ ከሰብዓዊና ከዴሞክራሲያዊ መብቶች ዕጦት በተጨማሪ ለአስከፊ ድህነት የተዳረገ ነበር፡፡ አሁንም ድህነት ይጫወትበታል፡፡ ረሃብ፣ ማይምነት፣ በሽታ፣ ኋላቀርነትና የመሳሰሉት መርገምቶች የአገሪቱ መገለጫዎች ሆነው ዘመናትን ተሸጋግረዋል፡፡ ይህችን የመሰለች በቱሪዝም መስህቦች የታደለች አገር አልምቶ የምድር ገነት መፍጠር ሲቻል ሲኦል ውስጥ መኖር ይዘገንናል፡፡ ይብዛም ይነስም ከድህነት ውስጥ ለመውጣት ትግል በሚደረግበት በዚህ ዘመን፣ በቱሪዝም ዘርፍ ውስጥ የሚታዩትን ችግሮች መንግሎ ለመጣል አለመቻል ያስጠይቃል፡፡ ሁሌም ዘርፉ ውስጥ የሚታዩትን ችግሮች ከማውሳት ይልቅ በጥናት ላይ የተመሠረተ መፍትሔ ማመንጨት ይመረጣል፡፡ ደካማ መዋቅርና ብቃት የሌላቸው ሰዎች ይዞ ውጤት መጠበቅ ይብቃ፡፡ መሠረታዊ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡
የአገሪቱ ቱሪዝም ችግሮች ሲነሱ የመሠረተ ልማቶች አለመሟላት፣ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሠራሮች አለመስፈን፣ ቱሪስቶችን በብዛት ለመሳብ አለመቻል፣ የተወዳዳሪነት ብቃት አለመፈጠር፣ ባለሙያ በሚባሉትም ሆነ በማኅበረሰቡ ውስጥ በቂ ግንዛቤ አለመኖር፣ የሚመለከታቸው አካላት ተቀናጅቶ ለመሥራት አለመቻል፣ በመስህቦች አካባቢ በዘፈቀደ የሚደረጉ የዋጋ ጭማሪዎች መበራከት፣ በዘርፉ የሠለጠኑ ብቁ ባለሙያዎች በሚፈለገው መጠን አለመኖር፣ ለቅርሶች የሚደረገው ጥበቃና እንክብካቤ አናሳነት፣ ፓርኮች በሕገወጦች መወረራቸው፣ የዱር እንስሳት ለአደጋ በመጋለጣቸው መሰደዳቸውና በአጠቃላይ ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ተፃራሪ የሆኑ ድርጊቶች መበራከታቸው ተደጋግሞ ይወሳል፡፡ ከዚህም አልፎ ተርፎ ኃላፊነት የማይሰማቸውና ደንታ ቢሶች ከሚፈጥሩት እክል በተጨማሪ፣ በዘርፉ ውስጥ ብቃት የሌላቸው ግለሰቦችና መዋቅሮች መኖራቸው ትልቁ ፈተና ነው፡፡ ይህንን ፈተና በወኔ ተጋፍጦ መሠረታዊ ለውጥ ማምጣት የግድ ነው፡፡
‹‹ኢትዮጵያ ምድረ ቀደምት›› የሚለው የቱሪዝም ልዩ መለያ የወጣው ያለምክንያት አይደለም፡፡ ይህች አገር የቅድመ ሰው ዘር መገኛ ናት፡፡ በሌላ በኩል በዓለማችን ዙሪያ በዓመት በመቶ ቢሊዮን ዶላሮች የሚገላበጥበት ቡና የተገኘው እዚህች ተዓምራዊ አገር ውስጥ ነው፡፡ የሰው ዘር ለመጀመሪያ ጊዜ እንደተገኘባት የተነገረላት አገራችን ኢትዮጵያ በቀደምትነቷና በጥንታዊነቷ ብዙ እየተባለላት፣ በታሪካዊና በተፈጥሮ መስህቦቿ ፀጋ ብዙ እየተነገረላት፣ በዚህ ዘመን እንደ ቀደምት ዘመናት ማንቀላፋት ኃጢያት ነው፡፡ የቱሪዝም አባት በመባል የሚታወቁት አንድ ተምሳሌታዊ ዜጋ በግል ጥረት ተዓምር መሥራታቸው እየታወቀ፣ በተቋማትና በሚመለከታቸው ወገኖች መካከል ተቀናጅቶ መሥራት አልተቻለም ሲባል ያሳፍራል፡፡ የዱር እንስሳት መጠለያዎች ያላግባብ ሠፈራ ሲፈጸምባቸውና የመስህብ አካባቢዎችን ለቱሪስቶች አመቺ ማድረግ አቅቶ ውዝግብ ሲፈጠር በተደጋጋሚ መስማት ያስደነግጣል፡፡ ጎረቤት አገሮች ከዱር እንስሳት ፓርኮች ብቻ ከኢትዮጵያ ልቀው ዳጎስ ያለ ገቢ ሲሰበስቡ፣ ለምን ብሎ አለመቆጨትና ለመሥራት አለመነሳት አስተዛዛቢ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት መሠረታዊ ለውጥ ያስፈልጋል፡፡
በኮንፈረንስ ቱሪዝምና በግለሰቦች ጥረት የሚገኝ እዚህ ግባ የማይባል ገቢ ላይ ብቻ ከማተኮር ይልቅ፣ ጠብሰቅ ባለ ፖሊሲ የሚመራ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ መንደፍ የግድ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ የቱሪዝም ባለሙያዎችና አማካሪዎች ጭምር በመታገዝ የአገሪቱን የቱሪዝም ሀብት እንዲመነደግ ማድረግ ይገባል፡፡ በዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ድጋፍ በዓለም ዙሪያ የአገሪቱን የቱሪዝም ሀብት ማስተዋወቅ ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፡፡ ችግሮችን ከማድበስበስ ይልቅ ፍርጥርጥ አድርጎ በመነጋገር በጥናት ላይ የተመሠረተ የውሳኔ ሐሳብ ማግኘት ግድ ይላል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመሩት ምክር ቤት የሚመለከታቸው በሚባሉ አካላት ስብጥር ብቻ መገደብ የለበትም፡፡ የባለዕውቀቶች ስብስብ (መማክርት) አስፈላጊነት ይታሰብበት፡፡
ከማይዳሰሱ ቅርሶች የአገሪቱን ሃይማኖታዊና ባህላዊ በዓላት ወደ ገንዘብ መቀየር ለምን አይቻልም? ከኢትዮጵያ ጋር ቁርኝት የፈጠሩ ዓለም በሚያጨበጭብላቸው ዝነኛ የሬጌ ክዋክብት አማካይነት በዓመት አንዴ ታላቅ የሙዚቃ ፌስቲቫል በማዘጋጀት ዓለምን ወደዚህ ለማምጣት ለምን አይሞከርም? የታላቁ የዓባይ ወንዝ መነሻ የሆነችውን ኢትዮጵያ ለዓለም አስተዋውቆ ቱሪስቶችን በብዛት ማምጣት ችግሩ ምንድነው? በታሪካዊውም ሆነ በተፈጥሯዊ የቱሪዝም ሀብቶች በዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ድጋፍ ከፍተኛ ቅስቀሳ በማድረግ አገሪቱን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ተነሳሽነቱ ለምን ይጠፋል? ለቱሪዝም እንቅፋት የሆኑትን ደካማ ቢሮክራሲና ብልሹ ድርጊቶች ከሥር ከመሠረታቸው ፈነቃቅሎ በመጣል፣ በዕውቀት ላይ የተመሠረተ አሠራር ማስፈን ከተቻለ ከቱሪዝም ሀብት የሚገኘው ገቢ አስገራሚ ዕድገት ይመዘገብበታል፡፡ እንዲህ ያለ አስደማሚ ሀብት ይዞ አለመሥራት መርገምት ነው፡፡ እንደ ስሙና እንደ መለያው ሥራው ያማረ እንዲሆንና ስም ተሸካሚ ላለመሆን መነሳት ያስፈልጋል፡፡ አለበለዚያ ‹‹ኢትዮጵያ ምድረ ቀደምት›› የሚለውን ልዩና አስደማሚ መለያ አንግቦ የዘመናት ችግርን ማነብነብና ማንቀላፋት በታሪክ ያስጠይቃል!