‹‹ሰዎች ዶሮዎቼን ሊሰርቁ ይችላሉ፤ ሰዎች በጎቼን ሊሰርቁ ይችላሉ፤ ዕድሜዬን ግን ሊሰርቁ አይችሉም፡፡››
በቅርቡ ያረፈው የረዥም ርቀት ንጉሡ፣ ‹‹ይፍጠር ዘሺፍተር››- ማርሽ ቀያሪው ምሩፅ ይፍጠር፣ ‹‹ይፍጠር ዘማስተር››- ጌታው ይፍጠር፣ ከሦስት አሠርታት በፊት ለዜና አውታሮች የተናገረው፡፡ በ1972 ዓ.ም. በተካሄደው የሞስኮ ኦሊምፒክ በሁለት ርቀቶች በ5 ሺ እና 10 ሺ ሜትር ድርብ ወርቅ ማግኘቱን ተከትሎ፣ ምሩፅ በኦሊምፒክ ሲያሸንፍ ዕድሜው 36? ፣ 40?፣ ወይስ 42? ተብሎ የተለያዩ መረጃዎች መውጣታቸውን ተከትሎ በዘይቤ የሰጠው ምላሽ፣ በተለያዩ የኦሊምፒክና የአትሌቲክስ ታሪካዊ ድርሳናት ሰፍሮ ይገኛል፡፡ የሻምበል ምሩፅ ዜና ዕረፍት ከካናዳ ቶሮንቶ ታኅሣሥ 13 ቀን 2009 ዓ.ም. መሰማቱን ተከትሎ የሐዘን መግለጫ ካስተላለፉት መካከል፣ ኢንተርናሽናል ኦሊምፒክ ኮሚቴና ኢንተርናሽናል አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር ይገኙበታል፡፡ በኢትዮጵያም ብሔራዊ አትሌቲክስ ፌዴሬሽንና ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ካወጡት የሐዘን መግለጫ ባሻገር፣ ብሔራዊ እግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ሰባተኛው ሳምንት የፕሪሚየር ሊጉ ጨዋታዎች በተካሄዱባቸው የአገሪቱ ከተሞች ምሩፅ ይፍጠርን በኅሊና ጸሎት ዘክረዋል፡፡ ስለ ምሩፅ በኩር አትሌትነት የሚያስታውሱ መግለጫዎችም ቀርበዋል፡፡
No comments:
Post a Comment