‹‹ኢትዮጵያ ንቂ…››
ኢትዮጵያውያን በተለያዩ ጉዳዮች በራሳቸው ይመካሉ፡፡
ከነሱም ሌላ በኢትዮጵያ የሚመኩ አሉ ብዙ ጥቁር ሕዝቦች፡፡ ከነዚህ ውስጥ ከሰሜን አሜሪካ በስተደቡብ በሚገኙ ደሴቶች ውስጥ የሚኖሩት
የዌስት ኢንዲያን ጥቁሮች ናቸው፡፡ በተለይም ደግሞ ጃማይካውያን፡፡ እነዚህ በራስ ተፈሪ ስም ራስ ተፈሪያን የሚባል ቡድን አቋቁመው
ኢትዮጵያ መመኪያ ሀገራቸው እንደሆነች ይከራከራሉ፡፡ አብርሃም በእግዚአብሔር ጥሪ ከከሃዲዎቹ ሀገር ከካራን ወጥቶ ወደ ተስፋይቱ
ወደ እግዚአብሔር ሀገር ወደ ከነዓን እንደሄደ የነሱም የተስፋ ምድራቸው ሀገር እግዚአብሔር ኢትዮጵያ እንደሆነች ይናገራሉ፡፡ ለዚህም
ነው በሕይወታቸውና የሕይወታቸው መግለጫ በሆነው በሥነ ጽሑፋቸው ውስጥ ኢትዮጵያ ገንና የምትገኘው፡፡
ዌስት ኢንዲያንስ ምንጫቸው አፍሪካ እንደሆነች
ያምናሉ፡፡ የማንነታቸው መገኛ እንደምትሆንም ይገምታሉ፡፡ በአ.አርዳቶርኔ መጽሐፍ ‹‹The scholar Man›› ውስጥ ያለው የዩኒቨርሲቲ
አስተማሪ አዳም ኩየስተስ የማንነቱን ጉዳይ አንስቶ ሲናገር ‹‹የራሴ ታሪክ ኖሮኝ እንዳደገ ሰው ስለራሴ ምንም ነገር አላውቅም፡፡ የማውቀው ያልሆንኩትን ብቻ
ነው፡፡ እንግሊዛዊ አይደለሁም እንደምገምተው እንዲያውም ዌስት ኢንዲያንም አይደለሁም›› ይላል፡፡ ትግሉ ማን እንደሆነ ለማወቅ ነው፡፡
በዚህ የማንነት ፍለጋ ውስጥ ነው አፍሪካ በተለይ
ደግሞ ኢትዮጵያ የማንነታቸው ተምሳሌት ሆና በየድርሰቶቻቸው ውስጥ የምትገለፀው፡፡ በሲልቪያ ዋይንተር በተጻፈው ‹‹The
Hills of Hebron›› በሚለው ድርሰት ውስጥ ፀጉሩ የተንዠረገገውና ፂማሙ ራስታ ሲታሠር በፖሊስ መኪና ፊት ተንበርክኮ በጥልቅ
ስሜት፤
ኢትዮጵያ ንቂ የልጆችሽንም ጩኸት አድምጪ
ኢትዮጵያ ዛሬ ነፃ ናት፤ የኛም ለቅሶ በምድሪቱ
ያስተጋባል
ኢትዮጵያ ንቂ፣ ንጋታችን በእጃችን ናትና፡፡
እያለ ይዘምራል፡፡ ‹‹The children of sisyphus›› በሚለው በኦርላንዶ ፓተርሰን ድርሰት ውጥ ያለው የራስ ተፈሪያውያን
መሪ ወንድም ሰሎሞን ደግሞ የኃይለሥላሴ መንፈስ እንዳደረበት ጥቁር ሙሴ ይቆጠራል፡፡ የራስ ተፈሪያውያን ተከታይ ሴቶች ስለኒህ የኢትዮጵያ
ንጉሥ እንደሚከተለው ይናገራሉ፡፡
‹‹በነሱ እኩይ መንገድ እኛን ሴቶችን ያረከሱንን
ነጫጮቹን ውሾችና ቡናማዎቹን ከሃዲዎች የእኛ ጥቁር አምላክ፣ እውነተኛ የእስራኤል ልጆች፣ የጥቁር ንጉሥ ሰለሞንና የጥቁሯ ንግሥት
ሳባ ዘሮች ያቃጥሉልናል፡፡
ይኸው ወንድም ሰለሞን ስለጥቁሮች በደል ‹‹አዎ
ወንድሞቼ! ነገር ግን አሁንም ከኛ የደበቁት ከሁሉም በላይ በጣም ጠቃሚ የሆነ ሌላ ነገር አለ፡፡ ይህም ያ ሰው አምላክ ነው፡፡
የራስ ተፈሪ መንፈስ ስለምንፈልገው በሁላችን ላይ አርፏል፡፡ ይህ ይህ ነው ወንድሞቼ ነጮቹ ሰዎች በእሱና በኛ ላይ የፈፀሙት የከፋ
ሀጢአት፡፡ ይህንንም ቡናማዎቹ አጋሮቻቸው አሁንም ያስተጋባሉ፡፡ በማለት ብቸኛው መፍትሔያቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለስ መሆኑን ይሰብካል፡፡
በዚሁ ገጽ ላይም ኢምፔሪያሊዝም ነጮችንም ጥቁሮችንም ባርያ እንዳደረጋቸውና እንግሊዝን ያገነናትና ለዚህ ያበቃትም የጥቁሮች ላብ
መሆኑን ይዘረዝራል፡፡
-
ገዛኸኝ ጌታቸው ‹‹ኢትዮጵያ በዌስት ኢንዲስ ሥነ ጽሑፍ›› (1992)
No comments:
Post a Comment