Thursday, September 22, 2016

የቱሪዝም ማስተር ፕላን አንድ አንጓ ሲመዘዝ



እንዴት ነው ነገሩ?

መሰንበቻውን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ጋር በመተባበር ለመጪዎቹ አሥር ዓመታት የቱሪዝም ኢንዱስትሪው የሚመራበትን ማስተር ፕላን ይፋ አድርጓል፡፡ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አምስት ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻዎች አንዷ እንድትሆን ለማድረግ ራዕይ ሰንቆ የተነሣው ሚኒስቴሩ ከ2006 ዓ.ም. ጀምሮ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
ሐምሌ 23 ቀን 2006 ዓ.ም. በተካሄደው የግብዓት ማሰባሰቢያ የምክክር መድረክ ላይ እንደተወሳው ማስተር ፕላኑ የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) ካዘጋጀው የቱሪዝም መሥፈርት ማስተር ፕላን (2013 - 2023) ጋር በተመሳሳይ የሚሠራ ነው፡፡
‹‹The Federal Democratic Republic of Ethiopia Sustainable Tourism Master Plan 2015-2025›› በሚባል የሚታወቀው ዐቢይ ሰነድ መሠረት በዐሠርት ውስጥ ሊተገበሩ ለታቀዱት ዕቅዶች 5.446 ቢሊዮን ብር ሊያስፈልግ እንደሚችል ተመልክቷል፡፡
ስትራቴጂካዊ ተግባራት ተብለው በ10 ዓይነቶች ለተዘረዘሩት እንደ መንደርደርያ የአገሪቱን ገጽታ፣ የቱሪዝሟን ጥንተ ታሪክ ባህላዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶችን፣ የኦሊምፒክ በተለይም አትሌቲክሱን የሚመለከቱ መጣጥፎች የሰነዱ አካል ናቸው፡፡
በተለያዩ ከተሞች በድሬዳዋ፣ መቐለና አዲስ አበባ ከዞናዊ ባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር መደረጉ፣ ረቂቅ ሰነዱም የተለያዩ ሒደቶችን አሳልፎ የመጨረሻው ደረጃ ላይ መድረሱ ያመለክታል፡፡
የመጀመሪያው ረቂቅ ከኅዳር 2006 ዓ.ም. እስከ መስከረም 2007 ዓ.ም. መከናወኑ በወሩም ለዐውደ ጥናት መቅረቡ፣ በተገኘው ግብዓት መሠረትም በጥቅምትና በኅዳር ሁለተኛው ረቂቅ መዘጋጀቱ፣ በማግስቱም በሁለተኛው ረቂቅ ላይ በቀረበ መግለጫና ውይይት መሠረት የመጨረሻው ሰነድ ኅዳር 5 ቀን 2007 ዓ.ም. መከናወኑ ተገልጿል፡፡
ከአንድ ዓመት ከዘጠኝ ወር በኋላ ሰነዱ ይፋ የሆነው በቅርቡ በኢሊሊ ሆቴል በተዘጋጀው መድረክ ነበር፡፡ የተለያዩ የምክክር መድረኮችን ያለፈው ሰነድ ልብ ያልተባሉ እንደ ክፍተት የሚቆጠሩ ነጥቦች እዚህ ላይ ይነሳሉ፡፡
ባለ 10 ዓመቱ ማስተር ፕላን የዘመን ማዕቀፍ ከ2015 እስከ 2025 እንደሆነ ያመለክታል፡፡ መነሻው ጃንዋሪ 2015 መድረሻው ዲሴምበር 2025 ከሆነ የዓመቱ ቁጥር 11 እንጂ 10 አይሆንም፡፡ የሰነዱ ቅድመ ዝግጅት ከኖቬምበር 2013 እስከ ኖቬምበር 2014 ዘልቋልና፡፡ መሆን የሚኖርበት 2015 – 2024 ወይም 2016 – 2025 ነው፡፡
የኢትዮጵያን ቱሪዝም የተሻለ ለማድረግ የተቀረፀው ማስተር ፕላን የመጨረሻ ምክክሩን በጥቅምት 2007 ሲያደርግ ሚኒስቴሩ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን የመጀመሪያ ዓመት (2008) ተግባራዊ ይደረጋል ማለቱ ይታወሳል፡፡ ማስተር ፕላኑ ይፋ የተደረገው ግን በዕቅዱ ሁለተኛ ዓመት ላይ ነው፡፡
እንዴት ነው ነገሩ?
የመግቢያው ፎቶ
በማስተር ፕላኑ ገጽ 16 ባለቀለም ፎቶ የሚያሳየው ሙክታር እድሪስ የተሰኘ አትሌት የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ይዞ ነው፡፡ የፎቶው መግለጫ ሙክታር ሐምሌ 7 ቀን 2004 ዓ.ም. በባርሴሎና በተካሄደው የዓለም ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ5000 ሜትር ማሸነፉን ያሳያል፡፡ ለዚህ ፎቶ መለጠፍ ምክንያቱ ግን ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በኦሊምፒክ ጨዋታዎች መሳተፍ የጀመረችበት እ.ኤ.አ. 1956ን ለማጀብ ነው፡፡
የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ፎቶ እንዴት የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ፎቶን ይገልጻል? ከኢትዮጵያ አልፎ በጥቁር አፍሪካውያን ዘንድ በሮም ኦሊምፒክ (1960) የመጀመሪያው የኦሊምፒክ ባለወርቅ ለዚያውም በባዶ እግሩ ሮጦ ያሸነፈ፣ ከአራት ዓመት በኋላ በቶኪዮ የዓለምንና የኦሊምፒክ ክብረወሰኖች የሰባበረው አበበ ቢቂላ ፎቶግራፍ ጠፍቶ ነው? ለነገሩ መጣጥፉ አበበ ቢቂላ በቶኪዮ ‹‹የኦሊምፒክ ሪከርድ አሻሻለ›› ብቻ ነው ያለው፡፡  እንዴት ነው ነገሩ?
ሩጫ በኢትዮጵያ (Running in Ethiopia) የሚለው ንኡስ ምዕራፍ አገሪቱ በርካታ ሻምፒዮኖችን ከበኩሩ አበበ ቢቂላ ጀምሮ ማፍራቷን በመግለጽ ይጀምራል፡፡ መጣጥፉ ከአበበ ቢቂላ በቀጥታ የተሻገረው ወደ ኃይሌ ገብረሥላሴና ቀነኒሳ በቀለ፤ መሠረት ደፋርና ጥሩነሽ ዲባባ ነው፡፡ ምሰሶዎቹ አትሌቶች በሜልቦርን (እ.ኤ.አ. 1956) ፋና ወጊዎች መካከል ለስኬት የበቃው በሜክሲኮ ኦሊምፒክ (1968) በማራቶንና በ10ሺ ሜትር የወርቅና ብር ሜዳሊያ አሸናፊው ማሞ ወልዴ፣ በሞስኮ ኦሊምፒክ (1980) በ5ሺና 10ሺ የሁለት ወርቅ አሸናፊ በመሆን የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊና አፍሪካዊ የሆነው ‹‹ማርሽ ቀያሪው›› ምሩፅ ይፍጠር፣ የመጀመሪያዋ አፍሪካዊት በባርሴሎና ኦሊምፒክ (1992) 10ሺ ሜትር ባለወርቅ ኢትዮጵያዊት ደራርቱ ቱሉ፣ በአትላንታ ኦሊምፒክ (1996) የመጀመሪያዋ አፍሪካዊት የማራቶን ባለወርቋ ፋጡማ ሮባ ለምን ተረሱ?
ከምክክሩ መድረክ የኦሊምፒክ ኮሚቴ ለምን አልተጋበዘም? በወቅቱ የነበረው ስፖርት ኮሚሽንስ? እንዴት ነው ነገሩ?
ኢትዮጵያን ለቱሪስት መዳረሻነት ከሚያነቃቁት ነገሮች መካከል በዩኔስኮ (የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት) በዓለም ቅርስነት የተመዘገቡት ባህላዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ይጠቀሳሉ፡፡ ዘጠኝ በማስመዝገብ ከአፍሪካ ቀዳሚ ናት፡፡ የማስተር ፕላን ሰነዱ እነዚህን በአግባቡ ጠቅሷቸዋል፡፡ ጊዜያዊ መዝገብ (ሊስት) ውስጥ የተያዙ አምስት ቅርሶችም ተመልክተዋል፡፡ ለዚህም የረዳው የዩኔስኮ ድረ ገጽ መሆኑም አይሳትም፡፡
ከግዙፍ ቅርሶች ሌላ ረቂቅ/ኢንታንጀብል ባህላዊ ቅርሶች በሰው ልጅ ወካይ ቅርስነት በ2006 ዓ.ም. የተመዘገበው የመስቀል በዓል በሰነዱ ቢመለከትም፤ በ2008 ዓ.ም. ሁለተኛው ወካይ ቅርስ ሆኖ የተመዘገበው የሲዳማ ባህላዊ የዘመን መለወጫ ‹‹ፊቼ ጫምባላላ›› በሰነዱ አልተገለጸም፡፡ ሰነዱ ከዓመት በፊት መጠናቀቁ ቢታወቅም፣ ምናልባት ካልታተመ ማሻሻል አይቻልም ነበር?
እሱም ባይቻል? ጊዜያዊ መዝገብ ውስጥ ያሉት ለ2015 ፊቼ ጫምባላላ፣ ለ2016 የኦሮሞ ገዳ ሥርዓትና ኢሬቻ ተብሎ መጥቀስ ያልተቻለው ለምንድን ነው? በምክክሩ መድረክ ከቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን በተለይ ከዘርፉ ጋር የተያያዙ ባለሙያዎች አስተያየት እንዲሰጡበት ለምን አልተደረገም?
ኢትዮጵያ በዩኔስኮ ያስመዘገበቻቸው ዓይነተኛ ቅርሶች በሁለቱ ጎራ ብቻ የተመደቡ አይደሉም፡፡ የራሷ ፊደል፣ የራሷ አኀዝና ባለ 13 ወራት የዘመን አቆጣጠር ያላት ኢትዮጵያ መሆኗ በሰነዱ ለምን አልጎላም?
መጽሐፍ ቅዱስ ከተጻፈባቸውና ከተተረጐመባቸው ስድስት ቋንቋዎች አንዱ በሆነው በግእዝና በአማርኛ የተጻፉ ልዩ ልዩ ብራናዎች (ሰነዶች) መካከል 12ቱ በዩኔስኮ በዓለም ጽሑፍ ቅርስነት (Memory of the world Register) መመዝገባቸው እየታወቀ እንዴት የቱሪዝሙ ማስተር ፕላን ሳያካትተው ቀረ?
እነሱ ብቻም አይደሉም፤ የቀድሞው የመንግሥታት ማኅበር (ሊግ ኦፍ ኔሽንስ) ጥንታዊ ሰነዶች በዓለም ቅርስነት ሲመዘገቡ አንዱ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ (1923 - 1967) የፋሺስት ኢጣልያ የ1928 ዓ.ም. ወረራን በመቃወም በጄኔቭ ሸንጎ ፊት ያደረጉት ትንቢታዊና ታሪካዊ ንግግር ጽሑፍ ነበር፡፡ እንኳን ይሄ ሊካተት በብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሕፍት ኤጀንሲ የሚታወቁት 12ቱ የሚያስታውስ ከአዘጋጆቹ አንድ እንኳ እንዴት ጠፋ?
እንዴት ነው ነገሩ?
ለዘመናት ሲባል የኖረው የ3,000 ዓመት ታሪክ እንዴት እልፍ ማለት አቃተው? ባለፉት አሠርታት በተደረጉ ጥናቶችና ይፋ በሆኑ አርኪዮሎጂያዊ ግኝቶች ጥንታዊው የኢትዮጵያ ዘመን ከ4,000 ዓመታት በላይ መሆኑን በየሃ፣ በመነበይቲ፣ በውቕሮ (ትግራይ) የተገኙት ቁሳዊ ሀብቶች ተረጋግጧል፡፡ ከይሓና ከአክሱም በፊት የደአማት ሥርወ መንግሥት እንደነበረስ ይህን የሚያመለክት አካል አልተገኘም ይሆን?
አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማትና መስጊዶች (Timeless churches, Monasteries and Mosques) በተሰኘው ንኡስ ክፍሉም በላሊበላና በትግራይ የሚገኙት ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ከ13ኛው ምታመት ጀምሮ እንደታነፁ ይገልጻል፡፡ የላሊበላው በ12ኛው ምታመት መገባደጃና በ13ኛው ምታመት በነገሠው ቅዱስ ላሊበላ መሠራቱ ይታወቃል፡፡ የታሪክ ሰነዶች እንደሚያሳዩት በትግራይ የሚገኙት ከ120 በላይ የሚቆጠሩት ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ከአራተኛው ምታመት ጀምሮ በየምታመቱ መታነፃቸው ይወሳል፡፡
ከአዲስ አበባ ከተማ መስህቦች መካከል የቅርብ ዘመኑ ከ40 ዓመት በፊት በተደረገው የኢትዮ ሶማሊያ ጦርነት፣ እንደሰነዱ አገላለጽ በኦጋዴን ጦርነት የኢትዮጵያና ኩባ ወታደሮች መታሰቢያ የቆመው ትግላችን ሐውልት፣ ፎቶው ከነመግለጫው ታትሟል፡፡ ይሁን እንጂ በፀረ ቅኝ አገዛዝ ትግል የአውሮፓዊቷ ወራሪ ጣሊያንን በቅድሚያ ዓድዋ (1988 ዓ.ም.) ላይ ላንበረከኩት በኋላም በፋሺስት ጣሊያን ወረራ ጊዜ (1928-1933) ድል ለመቱት የኢትዮጵያ እርመኛ አርበኞች መታሰቢያ ከቆሙት ሐውልቶች አንዱን መጥቀስ ሳይቻል እንዴት ቀረ?
‹‹ነውን ለማወቅ ነበርን ጠይቅ ነውና!›› እንዴት ነው ነገሩ?

Friday, September 16, 2016

የጀግናው ምሩፅ ይፍጠር የጥቁር ዓባይ ኒሻን ዋጋው እምን ድረስ ነው?




በሔኖክ ያሬድ
 

ፎቶ መግለጫ


  1. ምሩፅ ይፍጠር በሙኒክ ኦሊምፒክ (1964 ዓ.ም.) በ5000 ሜትር ሳይወዳደር በተመለሰ በስምንት ዓመቱ (1972 ዓ.ም.) ሞስኮ ላይ ያጣጣመው ወርቃማው የኦሊምፒክ ድሉ
  2. በዱዞልዶርፍ በ1969 ዓ.ም. በተካሄደው አንደኛው የዓለም አትሌቲክስ ዋንጫ ምሩፅ ይፍጠር አፍሪካን በመወከል የተቀዳጀበት የ10000 ሜትር ድሉ
  3. በካናዳ በሕክምና ላይ የሚገኘው ምሩፅ ይፍጠር
ባለፈው ነሐሴ በሪዮ ኦሊምፒክ የ10 ሺሕ ሜትር ሴቶች ሩጫ ፍጻሜ ሲካሄድ አልማዝ አያና ከዚህ ቀደም ባልተፈጸመ አስደናቂ አሯሯጥ ዓለምን ባስደመመ መልኩ ድል ስትመታ፤ በተመሳሳይ ርቀት ከ36 ዓመት በፊት በሞስኮ ኦሊምፒክ ድል የመታው ምሩፅ ይፍጠር በፅኑ ሕመም በሆስፒታል ውስጥ ሆኖ ውድድሩንና የአልማዝን ድል ይከታተል ነበር፡፡ ‹‹በአልጋ ቁራኛ በደዌ ዳኛ ቢያዝም ምሩፅ ደስታውን ከመግለጽ አልተቆጠበም፡፡
ከ12 ዓመት በላይ በዓለም አትሌቲክስ አደባባይ በረዥም ርቀትና በግማሽ ማራቶን ተደጋጋሚ ድሉ በአሯሯጥ ስልቱ ማርሽ ለዋጩ ‹‹ይፍጠር ዘ ሺፍተር›› የተሰኘው ምሩፅ በካናዳ ሞንትሪያል በፅኑ ሕመም እየተሰቃየ በሆስፒታል ውስጥ ይገኛል፡፡
በአሯሯጥ ስልቱ ዓለም ጉድ ያለለት ምሩፅ ከአንድ ዓመት ወዲህ በሳምባው ላይ በደረሰ ጉዳት በካናዳ ሕክምናውን እየተከታተለ ቢቆይም ፈውስ አላገኘም፡፡ ሁለቱም ሳምባዎቹ በመጐዳታቸው ምክንያት በተገጠመለት የመተንፈሻ አካል (ኦክሲጅን) አማካይነት ነው እየኖረ ያለው፡፡
እነዛ ማርሽ ይቀያይሩ የነበሩት ተወንጫፊ እግሮቹ ዊልቸር ላይ መዋላቸውም እየተነገረ ነው፡፡
ጋዜጠኛ ደረጀ ኃይሌ ‹‹በደራው ጨዋታ›› በተሰኘው የራዲዮ መጽሔት ፕሮግራሙ ምሩፅን ከነበረበት ሆስፒታል በስልክ ባነጋገረበት ጊዜ ምሩፅ ሳምባዎቹ ከጥቅም ውጪ ሆነው በኦክሲጅን እየተነፈሰ ‹‹ሕዝብ ኢትዮጵያ ጸልዩልኝ›› ሲል መናገሩ ተሰምቷል፡፡
ከሆስፒታል ወጥቶ በሌላ የጤና ማዕከል በኦክሲጅን ድጋፍ ክብካቤ እየተደረገለት ላለው ምሩፅ ይፍጠር ከነሐሴ መገባደጃ ጀምሮ ብሔራዊ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የ200 ሺሕ፣ ብሔራዊ ኦሊምፒክ ኮሚቴ የ150 ሺሕ፣ ወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር የ250 ሺሕ ብር፣ በድምሩ የ600 ሺሕ ብር ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል፡፡ በተለይ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ፣ ችግር የደረሰባቸው ወገኖቹን በመርዳት የሚታወቀው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከአትሌቱ ጐን በመሆን አጋርነቱን እንዲያሳይም ጠይቋል፡፡
ምሩፅ ይፍጠር ሲገለጽ
መስከረም 1961 ዓ.ም. አበበ ቢቂላና ማሞ ወልዴን የያዘው የሜክሲኮ ኦሊምፒክ ተሳታፊ አትሌቶች የመጨረሻ ጉዟቸውን ወደ ሜክሲኮ ሲቲ ከማድረጋቸው በፊት ለልምምድ ያረፉት አስመራ ከተማ ነበር፡፡ በአስመራ ንግሥተ ሳባ ስታዲየም ልምምድ ሲያደርጉ የተመለከተው የከተማዋ ነዋሪ ምሩፅ ይፍጠር ለወደፊት ሕይወቱ በር ከፋች አጋጣሚ ፈጠረለት፡፡ በልምምድ ሩጫ ውድድርም ከነማሞ ወልዴ ጋር ተወዳድሮ መጨረሻ ቢወጣም አሯሯጡንና አቅሙን ያስተዋሉት አሠልጣኝ ንጉሤ ሮባ በአየር ኃይል ስፖርት መምሪያ እንዲያዝና ልምምድ እንዲያደርግ አደረጉ፡፡ ቅጥሩንም ፈጸመ፡፡ ለ20 ዓመታት በአየር ኃይል ሲያገለግል እስከ ሻምበልነት ደርሷል፡፡
በአዲስ አበባው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ስታዲየም፣ ንብ የሚባለውን የአየር ኃይል ስፖርት ክለብን እየወከለ በብሔራዊ ሻምፒዮናና በጦር ኃይሎች ውድድር ውጤታማ መሆን የጀመረው ምሩፅ፣ የመጀመሪያው ኢንተርናሽናል ውድድሩ በ1962 ዓ.ም. በምሥራቅ አፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታንዛኒያ ውስጥ በ1,500 ሜትር ከኦሊምፒክ ባለወርቁ ኬፕቾግ ኬይኖ ጋር ተወዳድሮ ሦስተኛ የወጣበት ውድድሩ ነበር፡፡
በ1963 ዓ.ም. በአሜሪካ በተካሄደው የአፍሮ አሜሪካን ውድድር በ10 ሺሕ ወርቅ፣ በ5 ሺሕ ሜትር ብር ሜዳሊያ በማግኘት ድሉን አሐዱ ብሎ ጀምሯል፡፡
የመጀመሪያው የኦሊምፒክ መድረኩ በሆነው 20ኛው ኦሊምፒያድ በሙኒክ ሲካሄድ ምሩፅ በ5 ሺሕና በ10 ሺሕ ሜትር ለመወዳደር ነበር ወደ ሥፍራው ያመራው፡፡ በ10 ሺሕ ሜትር በማጣሪያው አንደኛ ወጥቶ በፍጻሜው ሦስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያን አግኝቷል፡፡ በ5 ሺሕ ሜትር ማጣሪያ በአሠልጣኞቹ ችግር ምክንያት በጊዜ ባለመድረሱ የተነሳ ሳይወዳደር በመቅረቱ ሌላ ሜዳሊያ የማግኘት ዕድሉ ተጨናግፎበታል፡፡
በ1965 ዓ.ም. በሌጎስ (ናይጄሪያ) በተካሄደው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች በ10 ሺሕ ወርቅ በ5 ሺሕ ብር አሸንፏል፡፡ በዚያው ዓመት ከሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ከተውጣጡት መካከል የኢትዮጵያ ስፖርት ኮከብ አትሌት ተብሎ የተመረጠው ምሩፅ፣ በ1968 ዓ.ም. በሞንትሪያል (ካናዳ) በተካሄደው 21ኛው ኦሊምፒያድ ያለ ጥርጥር በ5,000 እና በ10,000 ሜትር ሁለት ወርቅ ያገኛል ተብሎ ቢጠበቅም፣ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ስፖርታዊ ግንኙነት የነበራት ኒውዝላንድ ከሞንትሪያል ኦሊምፒክ ባለመታገዷ ምክንያት አፍሪካውያን አንካፈልም በማለታቸው ሳይወዳደር ተመለሰ፡፡
በሙኒክ ኦሊምፒክ ምሩፅን ያሸነፈው ፊንላንዳዊው ላሲ ቨረን ዳግመኛ ድሉን ምሩፅ በሌለበት አጣጣመ፡፡
ምሩፅ የኦሊምፒክ ወርቅ ሕልሙን ያሳካው በ1972 ዓ.ም. ሞስኮ ባስተናገደችው 22ኛ ኦሊምፒያድ ሲሆን በሁለቱም ርቀቶች ወርቁን ያጠለቀው ፊንላንዳዊውን ላሲ ቨረንን ድል በመምታት ነበር፡፡
በሞስኮ ኦሊምፒክ ሲሮጥ ዕድሜው የገፋው (በፓስፖርት ዕድሜው 36 ዓመቱ በተለያዩ ሚዲያዎች እስከ 42 የሚያደርሱት) ምሩፅ፣ በ1969 ዓ.ም. እና በ1971 ዓ.ም. በተካሄዱት የዓለም አትሌቲክስ ዋንጫዎች አፍሪካን በመወከል አራት ወርቅ ሜዳሊያ ሲያገኝ ተወዳዳሪዎቹን በቀደመበት ርቀት ያህል በሞስኮ አልደገመውም፡፡ ዕድሜው ገፍቷልና፡፡
በሁለቱ የዓለም ዋንጫዎች በ5,000 ሜትር ውድድሩ ሊያበቃ 500 ሜትር ሲቀር፣ በ10 ሺሕ 600 ሜትር ሲቀር ነበር ማርሽ ቀይሮ በማፈትለክ ያሸነፈው፡፡ በሞስኮ ኦሊምፒክ ግን በሁለቱ ርቀቶች እንደ ቅደም ተከተላቸው 200 ሜትርና 300 ሜትር ሲቀረው ነበር ማርሻ ቀይሮ ድል የመታው ምሩፅ በ1971 ዓ.ም. በዓለም ዋንጫ አፍሪካን ወክሎ ለመካፈል የበቃው የመጀመሪያው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በዳካር (ሴኔጋል) ሲካሄድ ሁለት ወርቅ (በ5 ሺሕና 10 ሺሕ) በማግኘቱ ነበር፡፡
ምሩፅ 1971 ዓ.ም. ወርቃማ ዓመቱ ነበር፡፡ እጅግ የገነነበት ታላቅ ክብርንም የተቀዳጀበት፡፡ በዚያው ዓመት በቼኮዝሎቫኪያ በተዘጋጀው የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ዘጠኝ አትሌቶች ሲመረጡ አንዱ ምሩፅ ሲሆን ‹‹የኮከቦች ኮከብ›› ተብሎ መመረጡ በተዘጋጀው የተሸላሚዎች መድረክ ራሱ ከመሃል በከፍታ መቀመጡ ይታወሳል፡፡ የወርቅ ጫማም ተሸላሚ ነበር፡፡ ምሩፅ ድርብ ድሎቹን በዳካር፣ በሞስኮና ሞንትሪያል በተደረጉ አህጉራዊና ዓለማዊ ውድድሮች ስድስት ወርቅ ይዞ አዲስ አበባ በደረሰ ጊዜ ጋዜጠኛ ኃይሉ ልመንህ እንዲህ ገጥሞለት ነበር፡፡
‹‹አብዮቱ ፈካ አበባው አማረ
ያለም ሻምፒዮና በምሩፅ ሠመረ፡፡
ሞስኮ ላይ ቀደመ ዳካር ላይ ድል መታ
ሞንትሪያል ደገመ እንዳመሉ ረታ
ዓለም ይሁን አለ ድሉን ተቀበለ
እየደጋገመ ምሩፅ ምሩፅ አለ፡፡››
የመጀመሪያ ዓለም ዋንጫ በዱዞልዶርፍ (ምዕራብ ጀርመን) ሲካሄድ አፍሪካን ወክሎ ለመሳተፍ የበቃው የቅርብ ተቀናቃኙን ኬንያዊውን የዓለም ሪከርድ ባለቤት ሔንሪ ሮኖን በመርታት ነበር፡፡
የዛሬ 40 ዓመት ምሩፅ ያለም ዋንጫ ክብርን በሁለት ወርቆች አጅቦ አዲስ አበባ ሲደርስ ጋዜጠኛ ንጉሤ አክሊሉም ስንኞች አስሮለት ነበር፡፡
‹‹አቦ ምናይነት ፍጡር ነው?
ድካም የማይሰማው
ለአፍሪካ ሁለት ወርቅ
ማስገኘት የቻለው
ምሩፅ ሮጠ ገሠገሠ
ዝናውን በዝና አደሰ
ሔደ ተራመደ እጅግ ፈጠነ
ገነነ በዓለም ገነነ
አሸንፎ ሲገባ
ዝናው በዓለም አስተጋባ››
በማለት ከዜማ ጋር ተቀናብሮ በሬዲዮ ቀርቦ ነበር፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት (የኅብረተሰብአዊት ኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ) ሻምበል ምሩፅ በቅድመ ሞስኮ ኦሊምፒክ ባገኛቸው አህጉራዊና ኢንተርናሽናል ድሎች ኢትዮጵያን ለታላት ግርማ ሞገስ በማብቃት ለፈጸመው አኩሪ ተግባር አምስተኛው የአብዮት በዓል ሲከበር ‹‹የጥቁር ዓባይ ኒሻን››ን ከርዕሰ ብሔሩ ሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም እጅ መቀበሉ ይታወሳል፡፡
በ1,500 ሜትር መወዳደር የጀመረው ምሩፅ 5 ሺሕና 10 ሺሕ መደበኛ ውድድሮቹ ቢሆኑም በጎዳና ላይ ሩጫዎችም ተደጋጋሚ ድሎች ማግኘቱ አይሳትም፡፡
በተለይ በተከታታይ ዓመታት ድል የተጎናፀፈበት የፖርቶ ሪኮ ግማሽ ማራቶን ውድድር ለዓለም ክብረ ወሰን የበቃበት ነበር፡፡ ጥር 29 ቀን 1969 ዓ.ም. በፖርቶ ሪኮ ኮዓሞ የ21 ኪሎ ሜትር (ግማሽ ማራቶን) ውድድር ምሩፅና መሐመድ ከድር ተከታትለው ሲያሸንፉ ምሩፅ የገባበት 1 ሰዓት 02 ደቂቃ 57 ሰከንድ ያለም ክብረ ወሰን ሆኖ ተመዝግቦለታል፡፡
በ1972 በፖርቶ ሪኮ ግማሽ ማራቶን አሸንፎ እንደተመለሰ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫም ‹‹የማተኩረው በሞስኮ ኦሊምፒክ ስለሆነ በፖርቶ ሪኮው ድሌ አልኮራም›› ማለቱ አይዘነጋም፡፡
በሞስኮ ኦሊምፒክ ለሦስተኛ ጊዜ ድሉን ለማጣጣም ቋምጦ የነበረው ፊንላንዳዊ ላሲ ቬረን በሞስኮ አየሩ ጥሩ ከሆነ እንደሚያሸንፍ መናገሩን ተከትሎ ምሩፅ በሰጠው አፀፋ ‹‹ሐሩርም ይሁን በረዶ እኔ ከማሸነፍ የሚገታኝ አንዳች ኃይል የለም›› ማለቱ ልበ ሙሉነቱን ያሳየበት አጋጣሚ ነበር፡፡
ከሞስኮ ኦሊምፒክ ድሉ በኋላ ጥንታዊ ኦሊምፒክ በተመሠረተበት ግሪክ ለኦሊምፒያዊ ሽልማት ከተመረጡ አምስት አትሌቶች ቀዳሚ ሆኖ የኦሊምፒክ ሎሬት አክሊልን ከርዕሰ ብሔሩ የተቀበለው ምሩፅ ይፍጠር ነበር፡፡
በዓለም ገናና ለሆነው ኃይሌ ገብረሥላሴና ለሞሮኮው ሰዒድ አዊታ አርአያ የሆነው ምሩፅ፣ ኢንተርናሽናል አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር በ1973 ዓ.ም. በምዕራብ ጀርመን ባደን ባደን ጉባኤውን ሲያካሂድ የዓለም አትሌቶችን ከወከሉ ሁለት አትሌቶች አንዱ ርሱ ነበር፡፡ ሁለተኛው ተወካይ እንግሊዛዊው ያሁኑ የኢንተርናሽናል አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር ፕሬዚዳንት የያኔው የሞስኮ ኦሊምፒክ የ1,500 ሜትር ባለድል ሰባስቲያን ኮ ነበር፡፡
ያ ስመ ገናና ‹‹ይፍጠር ዘ ሺፍተር››፣ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ከካናዳ ሆኖ በባዕድ መንግሥት እየታገዘ ያለውን ምሩፅ፣ እጅግ ውድና በገንዘብ የማይተመኑት ሽልማቶቹ በጨረታ ተሸጠው ለሕክምና እንዲውሉ ሲጠየቅ ‹‹ሽልማቶቼ የኢትዮጵያ ሕዝብ ናቸው፤ ለሽያጭ አይታሰቡም›› ያለውን ምሩፅ፣ ፍጡነ ረድኤት ሆኖ የሚደርስለት ማነው? ከኢትዮጵያ መንግሥት ከነሙሉ ክብሩ ጥቅሙና ግዴታዎቹ ጋር ያገኘው የጥቁር ዓባይ ኒሻን የሚያስገኝለትን ጥቅም የአሁኑ መንግሥት ለምን ችላ አለው? ብለው የሚጠይቁ አሉ፡፡
‹‹የፊት ወዳጅህን በምን ቀበርከው በሻሽ፣ የኋላው እንዳይሸሽ›› መባሉን እዚህ ላይ ማስታወስ ያሻል፡፡     



የምሩፅ ይፍጠር ዓበይት ድሎች
ኢትዮጵያን በመወከል
ሜዳሊያ
እ.ኤ.አ.
ኦሊምፒክ ጨዋታዎች
ወርቅ
1980
ሞስኮ
5,000 ሜትር
ወርቅ
1980
ሞስኮ
10,000 ሜትር
ነሐሰ
1972
ሙኒክ
10,000 ሜትር
መላ አፍሪካ ጨዋታዎች
ወርቅ
1973
ሌጎስ
10,000 ሜትር
ብር
1973
ሌጎስ
5,000 ሜትር
አፍሪካን በመወከል
የአይኤኤፍ ዓለም ዋንጫ (የዓለም አትሌቲክስ ዋንጫ)
ወርቅ
1977
ዱዘልዶርፍ
5,000 ሜትር
ወርቅ
1977
ዱዘልዶርፍ
10,000 ሜትር
ወርቅ
1979
ሞንትሪያል
5,000 ሜትር
ወርቅ
1979
ሞንትሪያል
10,000 ሜትር