25 January 2015
ተጻፈ በ
ሔኖክ ያሬድ
Saturday, January 24, 2015
Saturday, January 17, 2015
Tuesday, January 6, 2015
የገና ዛፍ ‹‹የገነት ዛፍ››?
የገና ዛፍ ‹‹የገነት ዛፍ››?
‹‹ከደነቶ እሙ ቈጽለ በለሶን›› [እናቱ የበለሶን ቅጠል አለበሰችው]
በሔኖክ ያሬድ
ከዓመታት በፊት የሶርያ ኦርቶዶክስ ቅዱስ ኒኮላስ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዩ የሆኑት አባ ዳንኤል ‹‹Christmas Tree … Pagan???- In Defence of the
Christmas Tree›› በሚል ርእስ አንድ መጣጥፍ አስነብበው ነበር፡፡ ከበርካታ ዓመታት በፊት በገና ሰሞን በአንድ ቴሌቪዥን ሃይማኖታዊ ፕሮግራም ሲተላለፍ ቀልባቸውን የወሰደው የውይይቱ ርእሰ ጉዳይ ከበዓል ጋር በተያያዘ የአንዳንድ ልማዶች አዝማሚያ በተለይም በወጣቶች ዘንድ የሚያሳድረውን ተፅዕኖ የሚመለከት ነበር፡፡
አባ ዳንኤል እንዳሉት ተወያዮቹ ‹‹የአዲሱ ዘመን›› (new
age) መንፈሳዊነት አደገኛነትን በተመለከተ ቢስማሙም ከመሃል አንዱ ተወያይ ያነሣው ‹‹… የገና ዛፍም እንዲሁ ከፓጋን (አሕዛብ) የተገኘ ነው፤›› የሚለው ነጥብ አስደንግጧቸዋል፡፡ እውን የገና ዛፍ የፓጋን ነው? ከልጅነታችን ጀምሮ የልደት በዓል በመጣ ቁጥር ስናከብር የምናደርገው የገና ዛፍ መሠረቱ በእርግጥ ከፓጋን ነው? የሚለውን አስተያየት መረመሩና ‹‹ፈጽሞ አይደለም፤ መሠረቱ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፤›› በማለት ማስረጃ እየጠቀሱ እንዲህ ጽፈውታል፡፡
ብዙዎች እንደሚገነዘቡት የገና ዛፍ ወደ አሜሪካ የዘለቀው ከጀርመን በተሰደዱ ዳያስፖራዎች ነው፡፡ ግን የዛፉ ምንጭ ከየት መጣ? ተወያዮቹ እንዳሉት ከፓጋኒዝም ነው? የገና ዛፍ መሠረት ከቀደምት ጀርመኖች አይደለም፤ በጥንታውያን ክርስቲያኖች ትውፊት በሥርዓተ ቅዳሴ ውስጥ የነበረና ከጊዜ በኋላ ከክርስትና የጠፋ ነው፡፡ በመካከለኛው ዘመን ከቅዳሴ በፊት ወይም በኋላ በምዕራብ አውሮፓ አብያተ ክርስቲያናት ይከናወን ነበር፡፡ በተለይም ከሰሙነ ሕማማትና ትንሣኤ ምስጢር ጋር የተያያዘ ነበር፡፡ ቆይቶም ከታዋቂ ቅዱሳን ጋርም መዛመድ ጀመረ፡፡ በታላላቅ ካቴድራሎች ዐውደ ምሕረት መንፈሳዊ ትርዒቱ
(Liturgical dramas) ይቀርብ ነበር፡፡
አንዱ ትርዒት እንደምዕራባዊቷ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት በገና ዋዜማ በሚከበረው የአዳምና ሔዋን በዓል ዕለትም ይቀርብ ነበር፡፡
‹‹የገነት ትርዒት›› (The Paradise play) በገነት ውስጥ በነበረው የአዳምና ሔዋን ታሪክ ላይ የተመሠረተ ነው፤ ይህው ከገነት ዛፍ፣ ወይም ከዕውቀት ዛፍ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ይህም የገነት ዛፍ በጀርመናውያን ዘንድ የታወቀና የተለመደ ሆኗል፡፡ በመሠረቱ ዛፎቹ የሚሸበርቁት በብስኩት (በሙልሙል) ሲሆን ቁርባንን የሚያስታውስ ነው፡፡ ቆይቶ ግን ልዩ ልዩ ጣፋጮች ተኩት፡፡
‹‹የገነት ትርዒት›› (The Paradise play) በገነት ውስጥ በነበረው የአዳምና ሔዋን ታሪክ ላይ የተመሠረተ ነው፤ ይህው ከገነት ዛፍ፣ ወይም ከዕውቀት ዛፍ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ይህም የገነት ዛፍ በጀርመናውያን ዘንድ የታወቀና የተለመደ ሆኗል፡፡ በመሠረቱ ዛፎቹ የሚሸበርቁት በብስኩት (በሙልሙል) ሲሆን ቁርባንን የሚያስታውስ ነው፡፡ ቆይቶ ግን ልዩ ልዩ ጣፋጮች ተኩት፡፡
የእኛ የገና ዛፍ የተገኘው ከፓጋን ‘ጥድ’ (Yule) ዛፍ ሳይሆን በአፕል በተጌጠውና ዲሴምበር 24 ቀን (ታኅሣሥ 28) በአዳምና ሔዋን በዓል ቀን ከሚደረገው የገነት ዛፍ ነው፡፡ የገና ዛፍ መሠረቱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው በማለት ያለጥርጥር አጽንዖት ይናገራሉ፡፡
ኢትዮጵያ እና የገና ዛፍ
በኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ጥድን ቆርጠው የገና ዛፍን በማዘጋጀት በዓሉን እያከበሩ ይገኛሉ፡፡ እንደ አውሮፓው ቅኝት ሁሉ እዚህም ከፓጋን (አሕዛብ) ሥርዓት የተወረሰ ነው ብለው የሚያምኑ ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡
የገና ዛፍ በ20ኛው ክፍለ ዘመን የመጀመሪያ ሩብ ውስጥ እንደነበረ የሰነድ ማስረጃ ቢኖርም ጊዜው መነሻ ነው ብሎ መደምደም ግን ሊያስቸግር ይችላል፡፡
ስለገና ዛፍ መሠረትም ምናልባትም በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ውስጥ ካለ ትውፊቶች ጋር ሊዛመድ የሚችልበት ነገር እንዳለ አንዳንድ ጽሑፎች፣ ድርሳኖች ይጠቁማሉ፡፡ ታላቁ ሊቅ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በ1920ዎቹ በጻፉትና ካለፉ በኋላ በ1948 ዓ.ም. በአለቃ ደስታ ተክለወልድ አማካይነት በታተመው ‹‹መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ›› ውስጥ ‹‹በለሶን›› የሚል ቃል እናገኛለን፡፡
‹‹በለሶን፡- ዕፀ አእምሮ [የዕውቀት ዛፍ] የገነት በለስ፤ አዳምና ሔዋን ፍሬውን በልተው ቅጠሉን የለበሱት ኋላም የልደት ዕለት በታምራት መልአክ አምጥቶላት ዳግሚት [ሁለተኛዋ] ሔዋን ለልጇ ለዳግማይ አዳም [ኢየሱስ] ያለበሰችው፤›› በማለት ቃሉን ይፈቱታል፡፡ ከቅዱስ ያሬድ ድጓ (የዜማ መጽሐፍ) የልደት ምንባብ ‹‹ከደነቶ እሙ ቈጽለ በለሶን›› [እናቱ የበለሶን ቅጠል አለበሰችው] በማለትም አክለውበታል፡፡
ስለ በለሶን አንድምታ የአለቃ ኪዳነ ወልድ ‹‹ሥላሴ ቅኔ›› እንዲህ ያፍታታዋል፡፡
‹‹በለሳ ገነት ለአዳም ወሔዋን መቲሮቶሙ
መንክረ ልደት አምላከ መንገሌሆሙ ሰሐበ፤
ወገብርኤልሀ ዜናዌ ቀጸበ፤
እንተ ከመ ዝሰ ግብር እምከመ ለአዳም ተውህበ
ወረከበት ሔዋን ዘኢተረክበ፤
ካዕበ ይስሐብ ኀቤሆሙ አበ
ለበለስ ይምትርዎ ካዕበ፡፡››
የቃል በቃል ፍችውም እንዲህ ነው፡፡ ‹‹የገነትን በለስ አዳምና ሔዋን መቁረጣቸው ወደነርሱ ሳባቸው፣ አስደናቂ የሆነውን የአምላክ መወለድ ወደነርሱ ሳበ፡፡ የምሥራች ነጋሪን ገብርኤልንም የጠቀሰው እርሱ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ነገር ምሥጢር ለአዳም እንደተሰጠ ሔዋንም ያልተገኘውንና ያልተመረመረውን ምሥጢር አገኘች፡፡››
በምዕራብም ሆነ በምሥራቅ ቤተ ክርስቱያን ትውፊት እንዳለው ሁሉ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም በአንዳንድ ዐበይት በዓላት እንደ ሆሣዕና፣ ስቅለት፣ ያሉት ከቅዳሴ በኋላ የሚደረጉ ሥርዓቶች አሉ፡፡ አንዱ በበዓለ ስቅለቱ ከስግደት በኋላ የሚደረገው በወይራ ቅጠል ካህኑ ‹‹ይኸን ያህል ስገድ›› እያለ የሚያደርገው ጥብጠባ ይጠቀሳል፡፡ ሊቃውንቱ ስለ በለሶን፣ ስለገና ዛፍ አንድምታ አፍታተው እንደሚነግሩን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
የሶርያው ካህን አባ ዳንኤል እንደጻፉት ገና ታላቁ ምሥጢረ ሥጋዌ የሚከበርበት ነው፡፡ በዚያም ምሥጢር እግዚአብሔር ቃል ሰው ኾነ፡፡ (ቃል ሥጋ ኮነ) በእኛም ዘንድ አደረ›› እንዲል፡፡ አባ ዳንኤል በጽሑፋቸው አያይዘውም፡፡ ‹‹በገና ዛፋችሁ ተደሰቱ›› ብለው አሳረጉ፡፡

Subscribe to:
Posts (Atom)